lunedì

በዓለም የተከሰተው የኤኮኖሚ ቀውስ

የሚያስከትለው የሥራ ችግር

ዶ/ር ዘለቀ እሬሶ

………አንድ ፀሐፊ በቅርቡ በዓለም እየተከሰተ ያለውን የኤኮኖሚ ችግር በሚመለከት እንዲህ በማለት ፅሑፉን ጀምሮ ነበር “የአሜሪካ ኢኮኖሚ ሲያስነጥስ የመላው ዓለም ኢኮኖሚ ጉንፋን ይይዘዋል”:: እውነትም ይህ የኤኮኖሚ ችግር እንደተላላፊ በሽታ ቀስ በቀስ ሐብታምና ደሀ አገር ሳይለይ ሁሉንም በማራወጥ ላይ ይገኛል::
………እንደሚታወቀው ሁሉ በአውሮፓ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ የውጭ ሀገር ዜጎች በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ሌሊትና ቀን ሳይሉ; ክረምት በብርዱ በጋ በሙቀቱ ሳይበገሩ; በየፋብርካው በመሰማራት ተገቢና ሕጋዊ በሆነ መንገድ በመሥራት ኑሮአቸውን እንደሚመሩ ይታወቃል:: በመሰረቱ ግባቸው እሩቅ፣ የያዙት ትግል መራራ፣ ችግራቸው ብዙ መሆኑን በተለይ በዚህ የኤኮኖሚ ችግር ወቅት በሚገባ የተረዱት ይመስላል፡፡ በቅርቡ በዓለም ላይ በተከሰተው የአኮኖሚ ቀውስ ሳቢያ አብዛኞቹ ከሰራተኛነት ለሥራ አጥነት በመብቃት የኑሮን መራራ ፅዋ በመቅመስ ላይ ይገኛሉ:: የባንክ ሥርዓት እየወደመ ነው፡፡ የንብረት ባለቤትነት ውሃ እየበላው ነው፡፡ በየቤተሰቡ ያለው ትልቁ ዜና አባት ወይም እናት ከሥራ ተባረርኩ ብለው ለቤተሰብ ሲያወሩ ነው፡፡ ሕዝቡ በያዘው ንብረት፣ በሚነዳው መኪና፣ በሚኖርበት ቤት፣ ባንክ ባስቀመጠው ገንዘብ ተማምኖ “የእኔ ነው” ብሎ መናገር እያቆመ ነው፡፡ ዛሬ የእሱ የነበረው ነገ ከእጁ እየወጣ ነውና፡፡ ባለው ኢኮኖሚ የከሰሩና የተበሳጩ ሚሊየነሮችና ቢልየነሮች ሕይወታቸውን ሲያጠፉም አልፎ አልፎ እየተሰማና እየታየ ነው፡፡ የጣሊያንም አገር ኢኮኖሚው ቀዝቀዝ ብሏል የውጭ ንግድ ተናግቷል የገንዘብ እንቅስቃሴም እየቀዘቀዘ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ከቀጠለም የሥራ አጦች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ይመጣል፡፡
………የአኮኖሚ ቀውሱ ምን ያህል ጊዜ እንደሚቆይ በትክክል መጥቀስ አስቸጋሪ ቢሆንም በአንድና በሁለት ወራት የሚፈታና ሊቃለል የሚችል ችግር እንዳልሆነ አብዛኞቹ የምጣኔ ሐብት ትምህርት ባለሙያዎች ይናገራሉ:: በጣሊያን አገር ከተወሰኑ አመታት ወዲህ ብዙዎች የውጭ ሀገር ዜጎች ለየድርጅቶች ተቀጥረው በመሥራት ፋንታ የራሳቸውን አነስተኛ ድርጅት በማቋቋም በመሥራት ላይ ናቸው:: የአኮኖሚ ችግሩ በመጀመሪያ ደረጃ የሚያጠቃው እነኚህን ገና በሚገባ ሁኔታ ያልተጠናከሩትን አነስተኛ ድርጅቶችን ይሆናል ; በየሚኖሩባቸው ከተሞችም በየስብሰባው፣ በየምረቃው፣ በየዐውደ ጥናቱና በተለያዩ የዜና ማሰራጫዎች እንደሚነገረው የኢምግሬሽን የወደፊት ሁኔታ በአውሮፓ ብቻ ሳይሆን በሌሎችም አህጉር ቀላል እንዳልሆነ ነው፡፡ ብቻ ለማንኛውም በጎ በጎውን ማሰብ አይከፋም፡፡ ነገር ግን በጎ በጎውን በማሰብ ብቻ የሚመጣ ለውጥ አይኖርም፡፡ የውጭ ሀገር ዜጋው ሁሉ እንደየሥራ ዘርፉ በየሰራተኛ ማሕበር በመደራጀት ብዙ የመብት ጥያቄዎችን ማንሳት ይኖርበታል::



ሹመትና ቁመት በምኞት አይገኝም

የአሜሪካን ታሪካዊ የምርጫ ውጤት አስመልክቶ ከዶ/ር ዘለቀ እሬሶ ጋር የተደረገ ቃለ መጠይቅ

15 11 2008

………”The Change We Need” የሚል የመወዳደሪያ መፈክር የነበረው ባራክ ኦባማ ከአሜሪካ ውጭ ያሉ በርካታ ሀገራት በፕሬዝደንታዊ ፉክክሩ ወቅት ድጋፋቸውንና ተስፋቸውን ሲሰጡት እንደነበር ይታወቃል። የጥቁሩ ህብረተሰብ መሪ የነበረውና ለለውጥ ከፍተኛ ትግል በማካሄድ የታወቀው ማርቲን ሉተር ኪንግ ለነጭና ለጥቁር እኩልነት የነበረውን ከፍተኛ ሕልም ከአርባ አምስት ዓመት በኋላ አሜሪካ በኋይት ሐውስ ፕሬዝዳንት ባራክ ሁሴን ኦባማን በማስተናገድ ዕውን ለማድረግ ሰሞኑን በመዘጋጀት ላይ ትገኛለች።

ጥያቄ: ለመሆኑ ባራክ ኦባማ ማነው? አንተ በአፍሪካዊነትህ የምታምን ጥቁር እንደመሆንህ መጠን ኦባማ በመመረጡ ምን የተለየ የሚሰማህ ስሜት አለ?
ዶ/ር ዘለቀ: ኦባማ በአባቱ ኬንያዊ፣ በእናቱ ደግሞ ነጭ የአርባ ሰባት ዓመት ምሁር ሲሆን፣ በሀርቫርድ ዩኒቨርሲቲ በሕግ ሙያ ትምህርት አጠናቆ እንደነበር ይነገርለታል። አዎን እኔ ጥቁር ነኝ በጥቁርነቴ እንደማንኛውም ጥቁር ሁሉ በኦባማ መመረጥ አልተደሰትኩም ብዬ ብል ማንም ሊያምን የሚችለው ጉዳይ አይሆንም; ሆኖም ከኦባማ ጥቁርነት ይልቅ በይበልጥ ትኩረት የሰጠሁት በማኅበራዊ፣ በፖለቲካዊና በኢኮኖሚያዊ የወደፊት የሀገር አመራር መሰረታዊ ፕሮግራሙ ላይ ነው። ታዋቂው የሰብዓዊ መብት ተከራካሪውና በ1984 እና 1988 እ.ኤ.አ. የዴሞክራቲክ ፓርቲ እጩ ፕሬዝዳንት የነበረው ጄሲ ጃክሰን የኦባማ በፕሬዝዳንትነት መመረጥ ከመደሰቱ የተነሳ አልቅሷል።

ጥያቄ: ከምርጫው በፊት ከባራክ ኦባማና ከማኬይን የማንኛው ደጋፊ ነበርክ?
ዶ/ር ዘለቀ: እኔ ማንንም በስሜት ተነሳስቼ አልደግፍም፤ ነገር ግን ኦባማ እሠራዋለሁ ብሎ ከተነሳባቸው ጉዳዮች አንፃር፣ የተሻለ ወጣትና አስተዋይ ምሁር እንደመድሆኑ መጠን ካሁን ቀደም ከነበረው ከቡሽ የአመራር ስህተት ትምህርት ያገኘ መሪ እንደሚሆን ተስፋ አደርጋለሁ።

ጥያቄ: በአሜሪካ የምርጫ ታሪክ ጥቁር ለፕሬዝዳንትነት ለመጀመሪያ ጊዜ እንዴት ሊመረጥ ቻለ?
ዶ/ር ዘለቀ: በአሜሪካ ኦባማ ሊመረጥ የበቃው ከጥቁርነቱ ይልቅ ይዞት በተነሳው የለውጥ አጀንዳ ነው; ከአገሩም አልፎ እንደ ጀርመን ባሉ አገራት፣ ከፍተኛ ድጋፍ በማግኘት ታላቅ ሰው መሆኑን ማስመስከር እንደቻለ በመላው ዓለም ለማየት በቅተናል። በእርግጥ ኦባማን በብዛት የመረጠው አፍሮ አሜሪካዊው ክፍል ሲሆን ነጩም ክፍል ቢሆን በቆዳ ልዩነት ሳያምን በብዛት መርጦታል:: በሌላ በኩል ደግሞ አንዳንድ “አሜሪካ በጥቁር ተገዝታ ከምናይ ሞትን እንመርጣለን” ያሉ አክራሪ የነጭ ዘረኞችና እብሪተኞች ኦባማን ለማስገደል ሙከራም እንዳደረጉ በተለያዩ የዜና ማሰራጫዎች ለመስማት በቅተናል:: አሜሪካ ሰባዊ መብት የተከበረበት ትልቅ አገር መሆኑንም በዚህ ወቅት ለመላው ዓለም አስመሰከራለች::
ጥያቄ: ኦባማ ለአሜሪካ ሕዝብ ወደፊት ምን ይለውጣል ብለህ ትገምታለህ?
ዶ/ር ዘለቀ: ኦባማ ለአሜሪካ ህዝብ እሠራለሁ ብሎ ቃል ከገባቸው መካከል የሥራ አጥነት መቀነስ፣ የሕክምና ሁኔታን ማሻሻልና የትምህርት ፖሊሲው ከፍተኛ ግምት ሊያሰጠው ችሎአል ። ቀጥሎም በኔ አስተያየት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ካሁን በፊት ከነበረው የተሻለ ይሆናል የሚል እምነት አለኝ። በሌላ በኩል ደግሞ የኦባማ መመረጥ በዓለም ፖለቲካ ስላለው ጉዳይ ሪፐብሊካኖች በእስካሁኑ አመራራቸው ለደሃ አገሮች ዕርዳታ አደረግን የሚሉት ከሌሎች ትናንሽ የአውሮፓ ሀገራት ጋር ሲነጻጻር ዝቅተኛ መሆኑንና ዋነኛ ትኩረታቸው የፀረ-ሽብርተኝነት ጉዳይ ብቻ በመሆኑ ሀገሪቱ ከነርሱ ልታገኝ የሚገባውን ጥቅም አላገኘችም።

ጥያቄ: ከሪፐብሊካኖች ከዲሞክራቶች የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ለአፍሪካ ዬቱ ይጠቅማታል?
ዶ/ር ዘለቀ: ዴሞክራቶች በውጭ ጉዳይ ፓሊሲያቸው፣ ከሪፐብሊካኖች ብዙ ባይለዩም ዲሞክራቶች በኦባማ አማካይነት በአፍሪካ የሚከተሉት ፖሊሲ ከሪፐብሊካኖች የተሻለ ይሆናል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።

ጥያቄ: የኦባማ ዓላማና ፓርቲ ለዓለም ህዝብ ይጠቅማል? ይጠቅማል ካልክ በምን በምን?
ዶ/ር ዘለቀ: ኦባማና ዲሞክራት ፓርቲ ከእንግዲህ በኋላ አሜሪካንን የሚመሯት በኃይል ሳይሆን በዲፕሎማሲ መሆን አለበት። በዚህ መሠረት የኦባማ መመረጥ በዓለም ካለው ጉዳይ ጋር ብናያይዘው፣ እስካሁን ሪፐብሊካኖች ከሄዱበት የተሳሳተ መስመር የተሻለ እንደሚሆን መጠራጠር የለብንም; ይህም በዓለም ሰላም እንዲሰፍን አዲስ ምእራፍ ይከፍታል እላለሁ።

ጥያቄ: ብዙ ሰው የኦባማ መመረጥ ለደሃ አገሮች በተለይም ለኢትዮጵያ ምንም አይጠቅማትም ብሎ ይላል አንተስ በበኩልህ ምን ትላለህ?
ዶ/ር ዘለቀ: አሜሪካ ትልቅ የበለፀገች አገር እንደመሆንዋ መጠን ማንኛውም በአሜሪካ ውስጥ የሚካሄድ እንቅስቃሴና ለውጥ በተቀሩት አገሮች በተለይም በደሃ አገሮች ላይ ተፅእኖ ይኖረዋል። በእርግጥ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ለአሜሪካ ጥቅም እንጂ ለሌላ ሀገር ጥቅም ቅድሚያ ይሰጣል ተብሎ መታሰብ የለበትም።

ጥያቄ: ለመሆኑ ይህ በአሜሪካን የፈነደቀው ጮራ በአውሮፓ ወይንም በሌሎች አገሮችስ ወደፊት ሊያንፀባርቅ ይችላል?
ዶ/ር ዘለቀ: ለጥያቄህ መልሱ በቀላሉ አዎን ሊሆን አይችልም ምክንያቱም እያንዳንዱ አገር የራሱ የሆነ የእድገት ደረጃና ታሪክ አለው:: በሌሎች አገሮች ገና ረጅም ትግል ያስፈልጋል ለምሳሌ ጣሊያን አገርን ብንወስድ ህብረተሰቡ እንኩዋንስ ጥቁር ስልጣን ላይ ሊወጣ ቀርቶ የአንድ ማዘጋጃ ቤት ከንቲባ ሆኖ የምናይበት ጊዜ ቅርብ ሆኖ አይታየኝም:: በአሜሪካን ከረጅም ጊዜ በኋላ የተከሰተው በሌሎችም መደገሙ ግን የማይቀር ነው ለዚህም ነው አባቶቻችን ሲተርቱ “ሹመትና ቁመት በምኞት አይገኝም” ያሉት; መመኘት ብቻውን በቂ አይደለም:: በዚህ ምርጫ የአሜሪካን ህዝብ ባራክ ኦባማን በፕሬዝዳንትነት መምረጡ ለለውጥ ከልቡ ቆርጦ መነሳቱን የሚያስተምረን መሆን መቻል አለበት። ኦባማ በተለይም በከፍተኛ ሁኔታ የተጎዳውን የአሜሪካንን ኢኮኖሚ ያስተካክላል፣ የአሜሪካንን ከኢራቅ መውጣት ያረጋግጣል፣ በሀገር ውስጥ ያሉትን የማኅበረሰቡን ችግሮች ይፈታል ተብሎ ይጠብቃል።
መልካም ዘመነ ኦባማ ለሁላችን ይሁን
ጠያቂ አብርሃም ዘውዴ



ዛሬ ዓለም የሚደሰትበት ታሪካዊ ቀን ነው

እንኩዋን ደስ አለን

05.11.2008
(የግል አስተያየት)


………እስከመጨረሻው ደቂቃ ድረስ እውነት ይሆናል ብዬ ያልገመትኩት ነገር ደረሰ:: የዲሞክራሲን ውበት በአይኔ አየሁ:: ኦባማ ማሸነፍ ብቻ ሳይሆን በጣም በሰፋ ልዩነት ማሸነፉ እጅግ በጣም ያስገርማል:: በዲሞክራሲ እጦት ለሚማቅቁ ሀገራትም ተስፋ የሚሰጥ ነው:: የማይቻል የማይለወጥ ምንም ነገር እንደሌለ ያሳያልና! ጥቁር አሜሪካኖች እኩልነታቸው ከታወጀ ከ 50 አመት በአነሰ ጊዜ ይህን ቀን ለማየት በቁ:: ለመላው የጥቁር እዝቦች እኩልነት የታገለው የነጻነት አባት ማርቲን ሉተር ኪንግ የትግል ጉዋደኛ የነበረው ጄሲ ጃክሰን በዚህች ታሪካዊ ቀን ደስታውን በእንባዎቹ ነበር የገለጸው:: የእርሱ እምባ ለሀዘን ሳይሆን ለጥቁር ህዝቦች ደስታቸው የተነባ ነው :: ውስጤን የነካኝ እምባ ነው::
እራሱ ተፎካካሪው ማኬይን እንኩዋን ሽንፈትን በጸጋ መቀበሉ! አይ የዲሞክራሲ ውበቱ!!! መሸነፉንም ተቀብሎ አልፎ ተርፎ መልካም እድልን ሲመኝለት! ለእኔ በኢጣሊያ የእድሜዬ ቆይታ ውስጥ የመመረጥ እንኩዋን ባይሆን የመምረጥ ነጻነት የሚኖረኝ ጊዜ እንደሚደርስልኝ ተስፋ አለኝ...
ለማንኛውም ይህችን ቀን ለማየት ያበቃኝ አምላክ ምስጋና ይድረሰው! ለአዲሱ የአሜሪካ መሪም እግዚሀብሄር መላውን የስልጣን ዘመኑን ይባርክለት:: ስኬታማ እና ተወዳጅ መሪ እንዲሆን፣ ለሰዎች እኩልነት፣ መከባበር እና ለአለም ፍቅር የሚተጋ እንዲሆን ከልብ እመኝለታለሁ! ለዚህም እግዚአብሄር ይርዳው!
.

ተጨማሪ በጣም ደስ ስላለኝ!
06 . 11 . 2008


………ይገርማችኋል! ይሄ ታሪካዊ ቀን ምስሉ እንዳያመልጠኝ ብዬ ለመቅረጽ ቴሌቪዝኑ ጋር ተጠግቼ እሱ ሲናገር አጠገቤ እንዳለ አድርጌ ካሜራዬን አስተካክዬ ፎቶ ሳነሳው ነበር::
* ለልጅ ልጆቼ እንዳስተላልፈው ነዋ!!!
* ከስድስት ወር ባልተናነሰ ጊዜ ውስጥ እንቅልፌን አጥቼ ስከታተል የነበረው የአለም ህዝብ ቀለም ወደ አንድ የሚሆንበት ታሪካዊ ቀን የሚያመለክትልኝ ስለሆነ ነዋ!
* በያገሩ ስደት ወጥተን በነጮች የቀን በቀን ዘረኝነት ለምንፈተነው ሁሉ ጥሩ ምሳሌ ይሆንልኛል ብዬ ነዋ!
* ጥቁር እንደሰው አያስብም ብለው እስካሁን ድረስ ሽንጥ ገትረው ለሚከራከሩ አይምሯቸውን ያስቀይርልናል ብዬ ነዋ!
* በቀለም ንጻትና ጥቁረት ወይም ጠይምነት ለሚያምኑ ቀለም ምንም እንዳልሆነ ያስተምርልኛል ብዬ ነዋ!
* የአንድ ምዕራፍ መደምደሚያ ላይ የደረስንበት በመሆኑ የታሪክ መዝገብ ላይ ስለሚሰፍር ነዋ!
* አሜሪካ እዚህ ለመድረስ 300+ አመታት ሊታሰብ የማይቻል ጉዞ ያለፉባት ነገርግን ዛሬ ባርነት፣ እንግልት፣ የቆዳ ቀለም ልዩነት፤ ዘረኝነት፣ እንደሙሉ ሰው አለመቆጠር፣ ሊይንቺንግ፣ አረ ስንቱ!!!


ድህና ሁኑልኝ
አለምፀሀይ
በኢሜል የደረሰን ደብዳቤ
etiopiainitalia@yahoo.it




የጣሊያን እምግሬሽን ሕግና የአውሮፓ ስጋት

ከዶ/ር ዘለቀ እሬሶ
09/06/2008

“አንዴ ሌባ ካሉት ቢቆርብም አያምኑት”

………አውሮፓ በጣሊያን ሀገር ውስጥ ባለፈው ወቅት ተካህዶ የነበረውን የምርጫ ውጤትና ከምርጫው ውጤት በኋላ በመከሰት ላይ ያለውን የእምግሬሽን ችግር አስመልክቶ በየጊዜው ከተለያዩ አቅጣጫዎች በመቅረብ ላይ ባሉት አቤቱታዎች ስጋት እያደረበት በመምጣት ላይ መሆኑን ሰሞኑን መረዳት ተችሏል:: ለአውሮፓ ስጋትስ ምክንያቱ ምንድነው ብለን ብንጠይቅ መልሱ ያለምንም ማወላወል የጣሊያን የእምግሬሽን ጉዳይ ይሆናል:: ምክንያቱም ካሁን ቀደም በተለያዩ ወቅቶች ጠቃቅሼ እንደነበረዉ የጣሊያን ዜና ማሰራጫዎች ወቅታዊና መሰረታዊው ዜና “በጣሊያን የውጭ ሀገር ዜጋው መብዛትና ወንጀሉን“ የተመለከተ ሲሆን የዚህ አይነቱ ከእውነት የራቀ የጥላቻ ፕሮፖጋንዳ ዘመቻ በሰላም አንድ ላይ በመኖር ያለውን የአገሪቱን ዜጋና የውጭ ሀገር ዜጋውን እንደ አይጥና ድመት አይነት ኑሮ እንዲኖሩ በመገፋፋት ላይ ይገኛል:: በመሆኑም በአገሪቱ ዜጋና በውጭ ሀገር ዜጋው መካከል መፈራራት፣ መራራቅ፣ መለያየት፣ መጠላላት፣ መናናቅ፣ መወናጀል፣ እና የመሳሰሉት እየሰፉ በመምጣት ላይ ናቸው::
………አውሮፓ ካለፈው የታሪክ ሂደቱ መረዳት እንደሚቻለው በአንድ መልኩ ባጠቃላይ የሰው ልጅ ሰበአዊ መብት የሚከበርበት፣ እኩልነትና ፍትህ የሰፈነበት፣ ዘረኝነትና ፋሺዝምን የሚያወግዝ፣ ቅኝ ግዛትን የሚቃወምና ባጭሩ ግለሰብ ሁሉ ሊኖርበት የሚመኘው ክፍለ ዓለም ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ እነኚህን መሰረታዊ መብቶችን በመቃወም የዘረኝነት የመርዝ ችግኞች በአንዳንድ የአውሮፓ ሀገሮች ሲተከሉ እያየ የችግኞቹን ሥር ነቅሎ ለማጥፋት መሰረታዊ እርምጃ በመውሰድ ፋንታ እየሰማ አልሰማሁም የሚል አሮጌና ወደ ፊት መራመድ ሲገባው እንደ ግመል ሽንት ወደ ኋላ በመመለስ ላይ ያለ ክፍለ ዓለም ይመስላል::
………በጣሊያን ባሁኑ ወቅት በአገሪቱ በመነዛት ላይ ባለው የጥላቻ ፕሮፖጋንዳ ምክንያት አንዳንድ በፊት ሥራ የነበራቸዉ የዉጭ ሀገር ዜጎች ለሥራ አጥነት በቅተዋል፣ የመኖሪያ ፈቃድ (permesso di soggiorno) የነበራቸው የጊዜ ገደቡ ሲወድቅ ለማሳደስ የሚጠብቁት ወቅት በትንሹ ከስድስት ወር እስከ አንድ ዓመት ተኩል በመራዘም ላይ ይገኛል፣ በእስር ቤት የሚሰቃየው የውጭ አገር ዜጋ ቁጥር እጥፍ ያህል እየጨመረ ነው:: የጣሊያን አዲሱ መንግስትም የውጭ አገር ዜጋውን መብትና ግዴታ ጎን ለጎን ማየት ሲገባው የመብት ጉዳይ ሲነሳ ሁለት አይኑን በመጨፈን ግዴታውን በሚመለከት ሁለት አይኖቹን በማፍጠጥ እያስፈራራ ነው:: አውሮፓም ይህ ሁሉ ሰበአዊ መብት በጣሊያን መንግስት መጣሱን እየተመለከተ ከተባራሪ ቁራጭ ማስጠንቀቂያ በስተቀር ምንም አይነት የወሰደው እርምጃ የለም:: ጉዳዩ አንዴ ሌባ ካሉት ቢቆርብም አያምኑት ይሆን?…

Nessun commento: